ማህበራዊ ኃላፊነትን የመወጣት ተግባር!!
ብሔራዊ አልኮልና አረቄ ፋብሪካ ከበቅሎ ቤት ሰፈር ተወላጆችና ከዳግም ትንሳዔ ወንድማማቾች ማህበር ጋር በመሆን በአዲስ መልክ የተገነባውን የ፶ አለቃ ቸርነት መንገሻ እና የወ/ሮ ሸዋዬ መኖሪያ ቤት የድርጅቱ ዋና ሥራ አስፈፃሚን ጨምሮ ከፍተኛ የሥራ አመራር አባላት ፤የወረዳው አመራር ተወካዮች፤የብስራት ኤፍ.ኤም ራዲዮ ባለቤት አቶ መሰለ መንግስቱ፤የማህበሩ ተወካዮችና የአካባቢው ነዋሪዎች በተገኙበት አስመርቆ ለወ/ሮ ሸዋዬ አስረክቧል፡፡
በወቅቱም የድርጅቱ ዋና ሥራ አስፈፃሚ አቶ መሥፍን አባተ የብሔራዊ አልኮልና አረቄ ፋብሪካ በአልኮል መጠጡ ኢንዱስትሪ የሚገኝ የመንግሥት ልማት ድርጅት መሆኑንና ያለውን አንጋፋነትና ብቁ ተወዳዳሪነት በአጭሩ ለታዳሚዎች አብራርተዋል፡፡ በተጨማሪም ድርጅታችን በአገር አቀፍ ደረጃ ለገበታ ለሀገር፤ለሸገር ማስዋብ፤ለታላቁ ህዳሴ ግድባችን ፤ለሀገር መከላከያ ሠራዊት እና በማዕድ ማጋራት አማካኝነት ያደረጋቸውን በርካታ ድጋፎች ለአብነት ከመጠቀሳቸውም በላይ ለመካኒሳ አካባቢ ነዋሪዎች የተደረጉ የኮሚኒቲ ፖሊሲንግ ጽ/ቤት እና የኮብል ስቶን መንገድ ግንባታዎችን በተጨማሪ በምሳሌነት በመግለጽ ይህ ሥራም የማህበራዊ ኃላፊነት ተግባር ዋነኛ አካል መሆኑን በመጥቀስ ወ/ሮ ሸዋዬን እንኳን ደስ አለዎት በማለት መልዕክታቸውን አስተላልፈዋል፡፡
የድርጅታችን ምክትል ዋና ሥራ አስፈፃሚ በበኩላቸው ሥራው የፈጠራባቸውን ደስታ በመግለጽ ብሔራዊ አልኮልና አረቄ ፋብሪካ መሰል የማህበራዊ ኃላፊነት ተግባራትን ማከናወኑን አጠናክሮ እንደሚቀጥል በመጥቀስ የቤቱን ካርታ ለወ/ሮ ሸዋዬ በማስረከብ የእንኳን ደስ አለዎት በማለት መልዕክታቸውን በተጨማሪ አስተላልፈዋል፡፡
በዚህም ወቅት ለመኖሪያ ቤቱ ግንባታ ጉልህ አስተዋጽኦ ያደረጉ ድርጅቶችና የማህበሩ አባላት የዕውቅና ሰርተፍኬት የተበረከተላቸው ሲሆን የድርጅታችን ዋና ሥራ አስፈፃሚ አቶ መሥፍን አባተ እና ምክትል ዋና ሥራ አስፈፃሚ ወ/ሮ ኮከቤ ቁምቢ እንዲሁም አቶ ተረፈ ሶርሱ ይገኙበታል፡፡
ጥራት መለያችን ነው!!!
ብሔራዊ አልኮልና አረቄ ፋብሪካ